|
ጮክ ብለህ ተናገር ዳግማዊ ዳዊት
This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it
ልቤ እስከሚሸበር - መልካው እስኪናጋ ወፎች ግ … ር እስኪሉ -እስኪበተን መንጋ ጀግና እስከሚፎክር - ፈሪ እስከሚያመልጠው ልጆች እስኪሮጡ - መዓት መጣ ብለው ቄሱ እስከሚያማትብ - እስኪል “በሥላሤ” ሠባኪው እስከሚል - “በጌታ እየሱሴ” ሸኹ “ያ - አላህ” ብሎ - አዛን እስኪያሰማ
ሾፌሩ ለመሄድ - ለመቆም ሲያቅማማ እናት “ውይ!” እስክትል - ደረቷን ስትመታ ሌባ እስኪበረግግ - እስኪሮጥ በአፍታ እስከሚያስተጋባ - ሸንተረር ሸሎቆው ተራራና ወንዙ - ዛፉና ቁጥቋጦው ጮክ ብለህ ተናገር - እኔም ልበል አሜን እስካዳነ ድረስ - ሀገሬን ወገኔን ላይጠራ አይደፈርስ - ሣይጨልም አይነጋ በለው ተናገረው - መልካው እስኪናጋ። መነኩሴው ሲረሸን - ቤተመቅደስ ገብቶ ዔሎሄ ሀገሬ - ወገኔ እሚል ጠፍቶ ሚስት ስትገደል - ሥለባሏ ጮሃ ወገኔ በሥደት ሲሞት በበረሃ አዛውንት ሲታሰር - እህት ስትደፈር ፍትህ ስትዛባ - ኃይማኖት ስትሻር ዝምታው ምንድን ነው - ተናገር ላዳምጥህ ወርቅ ነው እሚነጥር - አንጥረው ተናግረህ።
የውንድምህ ግጭት - ያኮረፍክበቱ አያስደነግጥም - ቢታይም ውጤቱ ሀገር አያጠፋ - አይገድል ወገን “ያዝ … ያዝ” መባባሉ ማውራት ይህንን ለእኔ ይመስለኛል - ጊዜ ማባከን እንኳንስ የሰው ልጅ - እኩይ ምላስ ያለው ድንጋይም ይጋጫል - የማይናገረው። ይልቅ፤
ሠላምን ሥትሻ - ፍትህ እና መብት ፍቅርን በልብ ይዘህ - ስትል ለእኛ መንግሥት ይህን ስትጠይቅ - በአንተ በፈረደ አንተ ስትገነባ - እራሱ እየናደ ያለውን ታገለው - “መለስ” የሚሉትን ሀገር አፍራሽ ይጥፋ - ቅድሚያ ለእርሱ ይሁን።
ዝምታ ወርቅ ቢሆን - ቢያስከብር በወገን አክባሪው ሲገደል - ዝምታ ምን ይሆን? ድሮም ይባል ነበር - ለመሾም በመንበር ዝምታ አይሆነውም - ከመናገር በቀር መሾም አይገኝም - ደጃዝማችነቱ በመናገር ጥረት - የምትገኝቱ።
ግና፤
መቋመጥ ለመውጣት - ከሥልጣን ኮርቻ ላገር ሳይሞቱላት - ልክ እንደነ ባልቻ እንደነ አባ ታጠቅ - እንደነ አባ ዳኘው እንደነ አባ በዝብዝ - እንደነ አባ ዳጨው እንደነ አባ መላ - እንደነ አባ ውቃው እንደነ አባ ኮስትር - እንደነ አባ ነጋ እንደ ዘረዓይ ድረስ - እንደነ አብዲሳ አጋ ካላወጡ ወገን - ከጠላት መንጋጋ መናገር ቧልት ነው - የመለፍለፍ ዓመል ሐኪም የሚያሰኘው - ቃልቻ ወይ ፀበል
እና፤
ጮክ ብለህ ተናገር - እኔም ልበል አሜን እስካዳነ ድረስ - ሀገሬን ወገኔን አሳርግ ለፍትህ - ለሠላም ለመብት ለሀገር ብልፅግና - ለወገን ለአንድነት ላይጠራ አይደፈርስ - ሣይጨልም አይነጋ ጮክ ብለህ ተናገር - ዙፋኑ እንዲናጋ።
ዳግማዊ ዳዊት
This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it
ሐምሌ 2001 ዓ.ም.
|