ዋና ገጽ ኪነ-ጥበብ ግጥም ጮክ ብለህ ተናገር (ዳግማዊ ዳዊት)
 
ጮክ ብለህ ተናገር (ዳግማዊ ዳዊት) Print E-mail
User Rating: / 18
PoorBest 

ጮክ ብለህ ተናገር

ዳግማዊ ዳዊት This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it

ልቤ እስከሚሸበር - መልካው እስኪናጋ

ወፎች ግ … ር እስኪሉ -እስኪበተን መንጋ

ጀግና እስከሚፎክር - ፈሪ እስከሚያመልጠው

ልጆች እስኪሮጡ - መዓት መጣ ብለው

ቄሱ እስከሚያማትብ - እስኪል “በሥላሤ”

ሠባኪው እስከሚል - “በጌታ እየሱሴ”

ሸኹ “ያ - አላህ” ብሎ - አዛን እስኪያሰማ

ሾፌሩ ለመሄድ - ለመቆም ሲያቅማማ

እናት “ውይ!” እስክትል - ደረቷን ስትመታ

ሌባ እስኪበረግግ - እስኪሮጥ በአፍታ

እስከሚያስተጋባ - ሸንተረር ሸሎቆው

ተራራና ወንዙ - ዛፉና ቁጥቋጦው

ጮክ ብለህ ተናገር - እኔም ልበል አሜን

እስካዳነ ድረስ - ሀገሬን ወገኔን

ላይጠራ አይደፈርስ - ሣይጨልም አይነጋ

በለው ተናገረው - መልካው እስኪናጋ።

 

መነኩሴው ሲረሸን - ቤተመቅደስ ገብቶ

ዔሎሄ ሀገሬ - ወገኔ እሚል ጠፍቶ

ሚስት ስትገደል - ሥለባሏ ጮሃ

ወገኔ በሥደት ሲሞት በበረሃ

አዛውንት ሲታሰር - እህት ስትደፈር

ፍትህ ስትዛባ - ኃይማኖት ስትሻር

ዝምታው ምንድን ነው - ተናገር ላዳምጥህ

ወርቅ ነው እሚነጥር - አንጥረው ተናግረህ።

 

የውንድምህ ግጭት - ያኮረፍክበቱ

አያስደነግጥም - ቢታይም ውጤቱ

ሀገር አያጠፋ - አይገድል ወገን “ያዝ … ያዝ” መባባሉ ማውራት ይህንን

ለእኔ ይመስለኛል - ጊዜ ማባከን

እንኳንስ የሰው ልጅ - እኩይ ምላስ ያለው

ድንጋይም ይጋጫል - የማይናገረው።

 

ይልቅ፤

 

ሠላምን ሥትሻ - ፍትህ እና መብት

ፍቅርን በልብ ይዘህ - ስትል ለእኛ መንግሥት

ይህን ስትጠይቅ - በአንተ በፈረደ

አንተ ስትገነባ - እራሱ እየናደ

ያለውን ታገለው - “መለስ” የሚሉትን

ሀገር አፍራሽ ይጥፋ - ቅድሚያ ለእርሱ ይሁን።

ዝምታ ወርቅ ቢሆን - ቢያስከብር በወገን

አክባሪው ሲገደል - ዝምታ ምን ይሆን?

ድሮም ይባል ነበር - ለመሾም በመንበር

ዝምታ አይሆነውም - ከመናገር በቀር

መሾም አይገኝም - ደጃዝማችነቱ

በመናገር ጥረት - የምትገኝቱ።

 

ግና፤

መቋመጥ ለመውጣት - ከሥልጣን ኮርቻ

ላገር ሳይሞቱላት - ልክ እንደነ ባልቻ

እንደነ አባ ታጠቅ - እንደነ አባ ዳኘው

እንደነ አባ በዝብዝ - እንደነ አባ ዳጨው

እንደነ አባ መላ - እንደነ አባ ውቃው

እንደነ አባ ኮስትር - እንደነ አባ ነጋ

እንደ ዘረዓይ ድረስ - እንደነ አብዲሳ አጋ

ካላወጡ ወገን - ከጠላት መንጋጋ

መናገር ቧልት ነው - የመለፍለፍ ዓመል

ሐኪም የሚያሰኘው - ቃልቻ ወይ ፀበል

 

እና፤

 

ጮክ ብለህ ተናገር - እኔም ልበል አሜን

እስካዳነ ድረስ - ሀገሬን ወገኔን

አሳርግ ለፍትህ - ለሠላም ለመብት

ለሀገር ብልፅግና - ለወገን ለአንድነት

ላይጠራ አይደፈርስ - ሣይጨልም አይነጋ

ጮክ ብለህ ተናገር - ዙፋኑ እንዲናጋ።


 

ዳግማዊ ዳዊት This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it

ሐምሌ 2001 ዓ.ም.

 

 

አዲስ ዜናዎችና ጽሑፎች

 
Banner

በጽሑፍ መሳተፍ ለምትፈልጉ በሙሉ!

በማናቸውም ጉዳይ ላይ ያለዎትን ሃሳብ፣ አስተያየት፣ ትችት፣ ግጥም፣ ልብወለድ፣ … በማይክሮሶፍት ወርድ ፕሮግራም በዩኒኮድ ፎንት ጽፈው ከራስዎ ኢ-ሜይል ሳጥን ጽሑፎትን አያይዘው በኢ-ሜይል አድራሻችን 

ethiopiazare@gmail.com ቢልኩልን ለሥራችን ቅልጥፍና ይረዱናል።

ኢትዮጵያ ዛሬ