ዋና ገጽ ኪነ-ጥበብ ግጥም አረንጓዴ ሰው (ዳግማዊ ዳዊት)
 
አረንጓዴ ሰው (ዳግማዊ ዳዊት) Print E-mail
User Rating: / 7
PoorBest 

አረንጓዴ ሰው

ዳግማዊ ዳዊት (ጥቅምት 2002 ዓ.ም.) This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it

“ህዝባችን ተሰብሰብ - ለሰበሩ ዜና

ባለፀጋው ጻድቅ - መሆኑ ይሰማ

ይኸ ባለፀጋ - ይኸ ያገሬ ሰው

ይኸ ባለሆቴል - ይኸ ወርቅ አንጣሪው

የሥራ ዕድል ፈጥሮ - ልቤን አስደሰተው”

 

ብሎ ጋዜጠኛው - ፅፎ አነበብኩና

ስለዚህ ባለሀብት - ሃሴት አረግሁና

እኔም የበኩሌን - ለገስኩት ምስጋና

 

“አንደበት ይከፈት - ጆሮዎች ያዳምጡ

ለዚህ ባላፀጋ - ሽልማቶች ይምጡ

በል እግዜሩም ስማ - ፅድቅ ተለውጧል

ከዛሬ መነኩሴ - ባላፀጋ በልጧል

“ፀሐይ ትቁምለት - ትዘግይ ጨረቃ

ይኸ ባለፀጋ - እስኪል ድረስ በቃ

እስከሚበዛለት - ሀብቱ እስከሚስፋፋ

ሌሊቱም ቀን ይሁን - ብርሃን አይጥፋ።”

 

ብዬ ምስጋናየን - ሳዥጎደጉደው

ይኸ የአጎቴ ልጅ - የተበሳጨው

ከእኔ የተለየ - ሚስጥር ያውቅ ኖሮ

እንዲህ ሲል ነገረኝ - ሃሳቡን ቀምሮ።

 

“ለተራበ ማብላት - ለታረዘ ማልበስ

ታማሚ ማጽናናት - ለችግርም መድረስ

መጾም መፀለዩ - ቅንነት ማሰቡ

መች ሆኖ ተገኘ - የዛሬ ሰው ግቡ!

 

“ከደሃ ቀምቶ - ከደካማ ዘርፎ

ቢሞላ ቢተርፍም - ከመጠንም ተርፎ

ወርቅና አልማዝ ይዞ - ነዳጅ አስቆፍሮ

ሆኖ መገኘት ነው - ካለመጠን ከብሮ

ሰውን ሰው ያሰኘው - የለየው ዘንድሮ።

 

“የሰው ልጅ ሲፈጠር - በጌታዬ አምሳያ

ነበረ ለታላቅ - ለክብር ማሳያ

ዛሬ የሰው ልጆች - ወረቀትን ፈጥረው

ቁጥር ጽፈውበት - አንድ ሁለት ብለው

አረንጓዴ ቀለም - ቅርጻ ቅርጹን ስለው

ከራሳቸው በላይ - ለብር ክብር ሰጥተው

መኖር ጀምረዋል - ከሱ በታች ሆነው።

 

“መልኩን ሳፈላልግ - ጠይም ወይም ቀዩን

ቀረና የእርሱነት - መምሰል አምሳያውን

ንዋየ ፀሎቱ - ገንዘብ ሆኖ አምላኩ

አረንጓዴ ሆኗል - ባለፀጋው መልኩ።

 

“አንተን መሳይ መንጋ - እናንት ኋላ ቀሮች

ጠይምና ጥቁር-ቀይ … የምትሉ ሰዎች

የሰው ልጅ ውበቱ - የሚያምር ቁመናው

አረንጓዴ ሆኗል - የእርሱ ሁለመናው።

 

“ገንዘቡ ዳኛ ነው - ፖሊስም ጠበቃ

ኃይሉ ልክ የሌለው - ተቆጥሮ አያበቃ

ፍትህና ክብር - ገዥ በገንዘቡ

ይኸ ባለፀጋ - ባለ ወርቅ ቅቡ

ሕጻን ሴት ያገባው - ሕፃን እቁባቱ

የሰው ሚስት የቀማው - አድርጎት መብቱ

ሁሉ ሰው ጌታዬ - ብሎ የሚጠራው

እርሱን የሚያደንቅ - ጋሸ ጋዜጠኛው።”

 

ብሎ ተናገረ - ይኽ የአጎቴ ልጅ

ስለ አረንጓዴው ሰው - ለሁሉ እንደማይበጅ።

 

ትናንት ህጻን ሆኘ - ሳድግ በሰፈሬ

የሰው ልጅ መጠሪያው - ልዩ ነው ከዛሬ

አይደለ በልብሱ - በፀጋ በሀብቱ

አይደል በቁመናው - ተክለ-ሰውነቱ

አይደል በትምህርቱ - በዕውቀት ሊቅነቱ

ሰው በሰውነቱ - ሲለካ የማውቀው

ፍፁም ልዩ ነበር - ዛሬ ከምናየው።

 

አንገቱን ለፍትህ - አንደበቱ ለእውነት

ውሸትን የጠላ - ግፍን የሚጋፈጥ

ከክፉዎች ሸንጎ - ፈጽሞ የራቀ

አንቱ የተባለ - በሀገር የታወቀ

ነበር የሰው መልኩ - ለእውነት መቆሙ

ትናንት የምናውቀው - የሰው ልጅ መልካሙ

ዛሬ ተለየና - ውበት ተቀይሮ

ዓይናችን የሚያየው - ብር ሆነ ዘንድሮ።

 

እስኪመለስ ድረስ - ዓይንም ወደ ድሮው

ስንናፍቅ ከዋልን - ገንዘብን እንደሰው

እውነትም ይዛባል - ፍትህ ይሰወራል

ገንዘብ የሀገር ዳኛ - ጠበቃ ይሆናል

 

አንተ ጋዜጠኛ - አንተ ወሬ አቀባይ

እስኪ እንደ አጎቴ ልጅ - አንተም እውነቱን እይ

ያ ባለፀጋ ሰው - በዓለም የከበረ

እውነቱን አሰማን - ማን እንደነበረ?


ዳግማዊ ዳዊት

ጥቅምት 2002 ዓ.ም.

This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it

 

አዲስ ዜናዎችና ጽሑፎች

 


ኢሳትን ይርዱ!


በጽሑፍ መሳተፍ ለምትፈልጉ በሙሉ!

በማናቸውም ጉዳይ ላይ ያለዎትን ሃሳብ፣ አስተያየት፣ ትችት፣ ግጥም፣ ልብወለድ፣ … በማይክሮሶፍት ወርድ ፕሮግራም በዩኒኮድ ፎንት ጽፈው ከራስዎ ኢ-ሜይል ሳጥን ጽሑፎትን አያይዘው በኢ-ሜይል አድራሻችን 

ethiopiazare@gmail.com ቢልኩልን ለሥራችን ቅልጥፍና ይረዱናል።

ኢትዮጵያ ዛሬ