|
የሞት ዕኩልነት ዳግማዊ ዳዊት
This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it
እግዜር በፈጠረው - ሰማይና ምድር ተራራ ሸንተረር - ውቅያኖስ ባህር ያገባኛል ብሎ - ሰው ባለቤት ሆኖ - ድንበር አበጅቶ የከርሰ-ምድር ሀብት - በስፋት አካብቶ አንተ ከዚያ ወዲህ - አንች ከዚህ ወዲያ - ብሎ ተከፋፍሎ አንዱን እጅግ ደልቶት - ሌላው ተበድሎ ይኖራል ይሞታል - የመኖር-ሕግ ሆኖ።
አንዱ ባለፀጋ - የተትረፈረፈው ሌላው ምስኪን ደሃ - ይበላው ይጠጣው - ይለብሰው የሌለው
የዓለም መልክ ሆነና - ሕይወት ዥንጉርጉሩ የሰው ልጅ ይኖራል - ገንዘብ ሆኖ ነውሩ ንብረት በለጠና - ከሰብዓዊ ክብሩ።
ሠራዊት መንግሥታት - አቤት ብለውለት ሀብታሙ ይኖራል - ዓለም አድልታለት ከውሻ አንሶ ደሃው - ማጣቱ ወንጅሎት እሱም ኖረ ተብሏል - ዓለም አድማበት የሰው ልጅ ኅሊና - እንዲህ ተመሳቅሎ ፀጋን አመሥግኖ ድህነት ኮንኖ ለኃይል አቤት ብሎ ደካማውን ገድሎ ሕይወት ነው ይለናል - “መኖር” ስሙ ሆኖ።
ልክ እንደ እግዜር ሆኖ - ሰው ቢሠራውማ - ሰማይና ምድሩ ደሃና ደካማ ባልኖሩበት ነበር - ገና ከጅምሩ ጉልበታም ለብቻው - ልክ እንደሂትለር ሞልቶ ከተረፈው - ከባለፀጋው ጋር እኛ ብቻ እንኑር - ብሎ ባለን ነበር ዳሩ አምላክ ሆነና - የዚህ ዓለም ንጉሥ ደሃውም ሀብታሙም - ደካማና ኃይለኛ እኩል ባይወደስ የሞት ቀን ሲመጣ - ሰው ሲመለስ ከአፈር ዕኩል መሆናቸው - ያኔ ነው የማይቀር። እናም ሂሳብ ሳስብ - አንድና አንድ ደምሬ ዕልፍ አዕላፍ ብደርስ - ከአሃዱ ጀምሬ አራት ነጥብ ሳደርግ - ስንኝ ቋጥሬ መደምደሚያው ሆነ - የድምር ውጤቱ ዕኩል የሚሆነው - ሰው በሰውነቱ ሲሞት ብቻ ሆኖ - አፈርኩ በስሌቱ በአንድዬ እምላለሁ - ቀፈፈኝ እውነቱ።
ዳግማዊ ዳዊት
This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it
ሰኔ 2002 ዓ.ም.
|