ዋና ገጽ ኪነ-ጥበብ ግጥም የሞት ዕኩልነት (ዳግማዊ ዳዊት)
 
የሞት ዕኩልነት (ዳግማዊ ዳዊት) Print E-mail
User Rating: / 5
PoorBest 

የሞት ዕኩልነት

ዳግማዊ ዳዊት This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it  

እግዜር በፈጠረው - ሰማይና ምድር

ተራራ ሸንተረር - ውቅያኖስ ባህር

ያገባኛል ብሎ - ሰው ባለቤት ሆኖ - ድንበር አበጅቶ

የከርሰ-ምድር ሀብት - በስፋት አካብቶ

አንተ ከዚያ ወዲህ - አንች ከዚህ ወዲያ - ብሎ ተከፋፍሎ

አንዱን እጅግ ደልቶት - ሌላው ተበድሎ

ይኖራል ይሞታል - የመኖር-ሕግ ሆኖ።

 

 

አንዱ ባለፀጋ - የተትረፈረፈው

ሌላው ምስኪን ደሃ - ይበላው ይጠጣው

- ይለብሰው የሌለው

የዓለም መልክ ሆነና - ሕይወት ዥንጉርጉሩ

የሰው ልጅ ይኖራል - ገንዘብ ሆኖ ነውሩ

ንብረት በለጠና - ከሰብዓዊ ክብሩ።

 

ሠራዊት መንግሥታት - አቤት ብለውለት

ሀብታሙ ይኖራል - ዓለም አድልታለት

ከውሻ አንሶ ደሃው - ማጣቱ ወንጅሎት

እሱም ኖረ ተብሏል - ዓለም አድማበት

የሰው ልጅ ኅሊና - እንዲህ ተመሳቅሎ

 

ፀጋን አመሥግኖ

ድህነት ኮንኖ

ለኃይል አቤት ብሎ

ደካማውን ገድሎ

ሕይወት ነው ይለናል - “መኖር” ስሙ ሆኖ።

 

ልክ እንደ እግዜር ሆኖ - ሰው ቢሠራውማ - ሰማይና ምድሩ

ደሃና ደካማ ባልኖሩበት ነበር - ገና ከጅምሩ

ጉልበታም ለብቻው - ልክ እንደሂትለር

ሞልቶ ከተረፈው - ከባለፀጋው ጋር

እኛ ብቻ እንኑር - ብሎ ባለን ነበር

ዳሩ አምላክ ሆነና - የዚህ ዓለም ንጉሥ

ደሃውም ሀብታሙም - ደካማና ኃይለኛ እኩል ባይወደስ

የሞት ቀን ሲመጣ - ሰው ሲመለስ ከአፈር

ዕኩል መሆናቸው - ያኔ ነው የማይቀር።

 

እናም ሂሳብ ሳስብ - አንድና አንድ ደምሬ

ዕልፍ አዕላፍ ብደርስ - ከአሃዱ ጀምሬ

አራት ነጥብ ሳደርግ - ስንኝ ቋጥሬ

መደምደሚያው ሆነ - የድምር ውጤቱ

ዕኩል የሚሆነው - ሰው በሰውነቱ

ሲሞት ብቻ ሆኖ - አፈርኩ በስሌቱ

በአንድዬ እምላለሁ - ቀፈፈኝ እውነቱ።


ዳግማዊ ዳዊት

This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it

ሰኔ 2002 ዓ.ም.

 

አዲስ ዜናዎችና ጽሑፎች

 
Banner

በጽሑፍ መሳተፍ ለምትፈልጉ በሙሉ!

በማናቸውም ጉዳይ ላይ ያለዎትን ሃሳብ፣ አስተያየት፣ ትችት፣ ግጥም፣ ልብወለድ፣ … በማይክሮሶፍት ወርድ ፕሮግራም በዩኒኮድ ፎንት ጽፈው ከራስዎ ኢ-ሜይል ሳጥን ጽሑፎትን አያይዘው በኢ-ሜይል አድራሻችን 

ethiopiazare@gmail.com ቢልኩልን ለሥራችን ቅልጥፍና ይረዱናል።

ኢትዮጵያ ዛሬ