ዋና ገጽ ኪነ-ጥበብ ግጥም አዛለች ወደ ፓርላማ (የምርጫ ጭውውት)
 
አዛለች ወደ ፓርላማ (የምርጫ ጭውውት) Print E-mail
User Rating: / 8
PoorBest 

አዛለች ወደ ፓርላማ (የምርጫ ጭውውት)

ክፍል ሦስት

ዳግማዊ ዳዊት

ባላፈው መጋቢት - የአቦለት ቤተክሲያን

ጠጋ ብዬ ጠየቅሁ - ወረቀት ሲበተን

እንዲህ ይነበባል - በራሪው ወረቀት

ከላይ ምርጫ ብሎ - ከታች ንብ አለበት፤

 

አዛል ምርጫ ገባች- ሹርባ ተሰርታ

መረራ ጉዲናን - በድምፅ ልትረታ

ኢህአዴግ ፓርቲዋን - ወክላ ቀርባለች

ልማታዊቷ ሴት ምረጡኝ - ትላለች።

 

ፎቶውን አይቸ -

አንገቴን አቅንቸ

መፈለግ ጀመርኩኝ - አዛሉን ጓጉቸ።

መስቀል ሲሳለሙ - አየኋችውና - ለብሰው ጃኖ ኩታ

መንገዴን ቀጠልኩኝ - ከቆሙበት ቦታ።

 

“ዶ/ር አዛሉ! ዶ/ር …” - ብዬ ስጠራችው

የፌደራል - ፖሊስ ወገቤን ዠለጠው

“አተ… አታ ባለጌ” - ብሎ ሲጮህብኝ

መሬት ተሰንጥቃ - ትውጠኝ ተመኘሁኝ።

 

እኝህማ አዛሉ - እኔ የማውቃቸው

ጠላ ኮማሪዋ - አይደሉ እንዴ እሳቸው።

 

ፖሊስ ቢዠልጠኝ - በያዘውም ዱላ

ምን ሊባል - ይገባል ከብልግና ሌላ

እንዲህ ያለ - ጥሪ “ዶክተር!” ብሎ ማለት

ስድብ ብቻ ሳይሆን - ብልግናም አለበት

ከአንድም ሁለት ጊዜ - ለቀበሌ ሸንጎ

ራቦል ጥፌያልሁ - ለአዛለች ሽመኮ

 

ማንበብና መፃፍ - የማያውቁትን ሴት

ዱላ እማይበቃው ነው - ዶክተር ብሎ መጥራት

ፖሊስ አዋከበኝ - ዶለኝ ወኸኒ ቤት

አዋርዷል ተብዬ - ልማታዊቷን ሴት።

************

ሁለት ወር ታስሬ - የተፈታሁኝ ቀን

አሸነፉን ሰማሁ - አዛሉ መረራን።

 

የሰፈራችን ሹም - የወያኔው ኔጭ ሹም

እንዲህ አርጎ አሰማኝ - መቸም ጉድ አያልቅም።

 

“የሰፈር ወይዘሮ - የጠላ ኮማሪ

የትናንት ልማት ሴት - ሥራን አስተማሪ

ማንበብ መጻፍ ባይኖር - ማይምም ቢሏቸው

ሀገር መገንባትን - ዲሞክራሲ አውቀው

የመንግሥት አመራር - በደንብ ገብቷቸው

አዛሉ ዶከተሩን - ጥለው አሳይዋቸው

ፖለቲካ ሳይንስ - ዓለም አቀፍ ቢሉ

ዶክተር መረራ ነኝ - የታወቅሁት ቢሉ

መረራ ተረታ - ድል ሆነ በአዛሉ።

 

ወይዘሮ አዛለች ነች - የሆነች አንበሳ

እንግዲህ በጀ በል - አምቦም እጅ ንሳ።

 

አሜሪካን ሀገር ያለሽው ሂላሪ

ይልቅስ ነይና - ከአዛለች ተማሪ።”

በስጨትጨት ብየ - እልሄ መጣና

መናገር ጀመርኩኝ - ተራዬ ሆነና።

 

“ገና ዱሮ ነበር - ያኔ ሳይወጠን

አልነጋም ያልናቸው - የዛሬውን አይተን።

 

መለስ ወንፊት ሰፍቶ - ማበጠር አቅዶ

ልደቱ እህል ሆኖ - ኃይሉም ገብቶ ወዶ

ይኸው ተበጠረ - መረራም ወረደ

ግፍም ሕግ ሆነና - ውሸት ተለመደ።”

 

ብዬ ተናግሬ - ልጨምር ስሞክር

ስውር ፖሊስ ኖሮ - ከነጭ ለባሹ ጋር

ሽጉጡን አውጥቶ - እያንገራገረ - ማጅራቴን ይዞ

እስር ቤት ጨመረኝ - በመኪና አግዞ።


ዳግማዊ ዳዊት

ግንቦት 2002

This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it

 

አዲስ ዜናዎችና ጽሑፎች

 
Banner

በጽሑፍ መሳተፍ ለምትፈልጉ በሙሉ!

በማናቸውም ጉዳይ ላይ ያለዎትን ሃሳብ፣ አስተያየት፣ ትችት፣ ግጥም፣ ልብወለድ፣ … በማይክሮሶፍት ወርድ ፕሮግራም በዩኒኮድ ፎንት ጽፈው ከራስዎ ኢ-ሜይል ሳጥን ጽሑፎትን አያይዘው በኢ-ሜይል አድራሻችን 

ethiopiazare@gmail.com ቢልኩልን ለሥራችን ቅልጥፍና ይረዱናል።

ኢትዮጵያ ዛሬ