ድንቅ ያፍሪካ አትሌቶች የሚሰሩት ስራ መላውን ጥቁር ህዝብ እጅግ ስላኮራ፤
በየደረሱበት በየውድድሩ፣ ታሪክ እየሰሩ፣ ድል እያበሰሩ፤ የናት ምድራቸውን ስም ስላስከበሩ ለታላቅ ሽልማት ወደ አፍሪካ አዳራሽ በክብር ተጠሩ። ከዚያም ጋዜጠኛ- ተናግሮ አናጋሪ የወሬ ሱሰኛ፤ ወደ አንዱ አትሌት ቀርቦ አድናቆቱን ደልጾ ድምጹን አለዝቦ፤ ‘ጽናት በሚጠይቅ በረዥም ርቀት ታሸንፋላችሁ ሁሌም ያለጭንቀት፣ አምስት ሽ አስር ሺው ውጤቱ ቢያረካም ዱላ ቅብብሉስ ለምን አይሳካም?’ በማለት ጠየቀ። ታዋቂው አትሌትም በስሱ እየሳቀ ‘ቀን ከሌት በመስራት ጥረታችን ሰምሮ፣ ውጤታችን አምሮ በስካሁን ድላችን ረክቷል ህዝባችን ዌል.. እንግዲህ ደግሞ ዱላ ቅብብሉን- ለመሪዎቻችን’ ብሎ ተናገረ በዚህ ንግግሩም ሪከርድ ሰበረ። አቤል ካሳሁንና ማህሙድ እንድሪስ ካሳተሙት ‘ከ… እስከ’ የግጥም መድብል የተወሰደ
|