ዋና ገጽ ኪነ-ጥበብ ግጥም ዘፍናችሁ ቅበሩኝ (ዳግማዊ ዳዊት)
 
ዘፍናችሁ ቅበሩኝ (ዳግማዊ ዳዊት) Print E-mail
User Rating: / 5
PoorBest 

ዘፍናችሁ ቅበሩኝ

ዳግማዊ ዳዊት መስከረም 2002 ዓ.ም. This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it

ሰውን ሰው አሳዶ - ቢያሳጣው መድረሻ

ጭንቅ ብርክ አስይዞ - ፍፁም መተንፈሻ

 

ሚሊዮኖች ቢያልቁ - በረሃብ በበሽታ

ጦርነት ቢመረጥ - በሠላሙ ፋንታ

 

መስማማት ተጠልቶ - መናቆር ቢሞገስ

ቅደሱ ቢረክስ - ርኩሱም ቢቀደስ

ሕግ የጉልበት ሆኖ - ፍትህም ተጠልፎ

አስታራቂ ጠፍቶ - ዳኝነት ተገፍፎ

መስገብገብ ሕግ ሆኖ - ሙስና ተለምዶ

ቅጥፈት ተሞካሽቶ - እውነትም ተዋርዶ

ቀማኛን ሆነና - የሚሰማ ጆሮ

ቁብ የሚለው ጠፋ - የደሃን እሮሮ

እጥፍ ድርብ ሆነ - ሰቆቃው ጨመረ

ዓይኔን እንባ ሞላው - ልቤ ተሰበረ።

 

አንገቴን ደፍቸ - መሬትን እየጫርኩ

መሞት እንደምሻ - ለአምላኬ እየነገርኩ

ፀሎቴ ተሰምቶ - አርጎ ሰማይ

ሞቴ ደረሰልኝ - ይህን እንዳላይ።

 

ዛሬ መሄጃዬ - ተራዬ ነውና

ከየመንደራችሁ - በጠዋት ውጡና

ሸኙኝ ጨፍራችሁ - በዘፈን በዜማ

ሞትን መርጫለሁ ይህን ከምሰማ።

 

እናቴ አታልቅሽ - አይመታ ደረት

አባቴም አትተክዝ - እኔስ ልሂድበት

ትቸው የምሄደው - የምተወው ዓለም

ከሞት የባሰ እንጅ - የተሻለ አይደለም።

 

ፅድቅና ኩነኔ - ቢኖርም ባይኖርም

ለእኔ እዚህ መኖሬ - ከሞት አይሻልም

እኔስ በፈጠረኝ - እመካለሁና

ሕይወት ይኖረኛል - ገነት እንደገና።

 

አልያም …

ሚካኤል ከበሩ - ባይቀበለኝም

አቡዬን ተክልዬን - ላያቸው ባልችልም

ገነት መግባት ቀርቶ - ገሃነም ብወርድም

ቁርጥ ያጠግባልና - አማረ አላማረም

ከመሞት መኖርን - በፍፁም አልመርጥም

የዚህ ዓለም ኑሮ - የአምሳያዬ ግፉ

ሞትን አስመረጠኝ - ተሽሎኝ ማረፉ።

 

እናም አታልቅሱ - አልሰማ ዋይ ዋይታ

በምትኩ አሳዩኝ - ዘፈንና እስክስታ

ክራር ጽናጽሉ - ከበሮው ይመታ

በገና ይደርደር - አስራ ሁለት ተርታ

ይነፋ ዋሽንቱ - ሳክስፎን እምቢልታ

ወንዶቹ በሆታ - ሴቶቹ በእልልታ

የዛሬን - የዛሬን - እኔን ደስ እንዲለኝ

ማልቀሱን ተዉና - ዘፍናችሁ ቅበሩኝ።


 

ዳግማዊ ዳዊት መስከረም 2002 ዓ.ም. This e-mail address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it

 

አዲስ ዜናዎችና ጽሑፎች

 
Banner

በጽሑፍ መሳተፍ ለምትፈልጉ በሙሉ!

በማናቸውም ጉዳይ ላይ ያለዎትን ሃሳብ፣ አስተያየት፣ ትችት፣ ግጥም፣ ልብወለድ፣ … በማይክሮሶፍት ወርድ ፕሮግራም በዩኒኮድ ፎንት ጽፈው ከራስዎ ኢ-ሜይል ሳጥን ጽሑፎትን አያይዘው በኢ-ሜይል አድራሻችን 

ethiopiazare@gmail.com ቢልኩልን ለሥራችን ቅልጥፍና ይረዱናል።

ኢትዮጵያ ዛሬ